የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ እና የመሬት ይዞታ ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ ከሪል ስቴት አልሚዎች ወይም ከግለሰቦች ንብረት የገዙ ነዋሪዎች ሕጋዊ አሠራሩን በመከተል የባለቤትነት ዝውውራቸውን እንዲያጠናቅቁ ጥሪ አቅርበዋል።
ተቋማቱ ባወጡት ማስታወቂያ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ሲነሱ የነበሩ የተናጠል ካርታ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ የባለቤትነት ማረጋገጫ ሂደቱ መከናወን እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።
በማስታወቂያው እንደተጠቆመው በርካታ ዜጎች ከሪል ስቴት ኩባንያዎች ወይም ከግለሰቦች የመኖሪያና የንግድ ቤቶችን በውልና ማስረጃ በኩል የገዙ ቢሆንም፤ እስካሁን ድረስ ሕጋዊ የሆነውን የንብረት ስም ዝውውር ሳያከናውኑ በግዢ ውል ብቻ ለረጅም ጊዜ ሲቆዩ ተስተውለዋል።
ይህ አሠራር በመሠረታዊነት ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ያስታወቁት ተቋማቱ የባለቤትነት ዝውውር ሳያደርጉ መቆየቱ ለባለይዞታዎች ሕጋዊ ዋስትናን የሚጋፋ መሆኑን አስታውቀዋል።
በተለይም የተናጠል ካርታ ለማግኘት የሚፈልጉ ባለይዞታዎች የስመ ንብረት ዝውውርን እንደ አስገዳጅ ቅድመ ሁኔታ ማሟላት እንደሚጠበቅባቸው ተመላክቷል።
በዚህም ተቋማት ለተናጠል ካርታ ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት እንዲችሉ ባለይዞታዎች በመጀመሪያ ደረጃ በሕግ የተደነገገውን የባለቤትነት ዝውውር ማጠናቀቅ አለባቸው የተባለ ሲሆን ይህ ሂደት የንብረት ይዞታን ሕጋዊነት ከማረጋገጡም በላይ የወደፊት ውዝግቦችን ለመከላከል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል።
ባለይዞታዎች የዚህን አሠራር አስፈላጊነት ተረድተው ከሰኔ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ተጀምሮ ባሉት ተከታታይ ቀናት ውስጥ ማለትም እስከ ሰኔ 25/ 2018 ዓ.ም ድረስ በሚኖረው የጊዜ ገደብ ውስጥ ንብረታቸው በሚገኝበት ክፍለ ከተማ በሚገኙ የመሬት ልማትና አስተዳደር ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ወይም የመሬት ይዞታ ምዝገባና መረጃ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች በአካል በመቅረብ ሂደቱን እንዲያጠናቅቁ ተጠይቀዋል።
ከዚህ የጊዜ ገደብ በኋላ ሊያጋጥሙ የሚችሉ አስተዳደራዊ እና ሕጋዊ ችግሮችን ለመከላከል ሲባል ነዋሪዎች በተቀመጠው ቀነ-ገደብ ውስጥ ጥሪውን እንዲቀበሉ ቢሮው አሳስቧል።
በሌላ በኩል መሬትን በሊዝ፣ በምደባ ወይም በጨረታ የወሰዱ ባለይዞታዎች የሊዝ ክፍያቸውን በአስቸኳይ እንዲፈጽሙ ጥሪ ቀርቧል።
የከተማ መሬት ሊዝ ደንብ ቁጥር 162/2016ን መነሻ በማድረግ እንደተገለጸው የሊዝ ባለይዞታ ክፍያውን በየዓመቱ መክፈል ያለበት ሲሆን የሶስት ዓመት ውዝፍ እዳ ካለበት ከአራተኛው ዓመት ጀምሮ ቢሮው ንብረቱን በመውሰድና በመሸጥ ለውዝፍ እዳው መክፈያ የማዋል መብት አለው።
በከተማው ካቢኔ ውሳኔ መሠረት መሬት በምደባ ወይም በሊዝ የወሰዱ ባለይዞታዎች ዓመታዊ እና ውዝፍ የሊዝ ክፍያቸውን የያዝነው የሰኔ ወር ከመጠናቀቁ በፊት ማለትም እስከ ሰኔ 25/2018 ዓ.ም ድረስ መክፈል እንደሚጠበቅባቸው ቢሮው አሳስቧል።
ባለይዞታዎች ከዚህ የጊዜ ገደብ በኋላ ሊያጋጥሙ የሚችሉ አስተዳደራዊ እርምጃዎችን ለመከላከል ሲባል ክፍያቸውን በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በአካል በመቅረብ እንዲፈጽሙ ቢሮው አስታውቋል።
ቢሮው የዜጎችን ንብረት ደኅንነት ለመጠበቅና የመሬት ይዞታ ምዝገባን ዘመናዊ፣ ግልጽ እና ቀልጣፋ ለማድረግ እየሰራ እንደሚገኝ የገለጸ ሲሆን ይህም የከተማዋን መሬት በአግባቡ ለማስተዳደርና ሕገ-ወጥ አሠራሮችን ለመከላከል የሚደረግ ጥረት አካል መሆኑን አክሏል።