ከአዲስ አበባ ውጪ በሚገኙ ሌሎች ክልሎች ተግባራዊ ሳይደረግ በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ በመተግበሩ በአሽከርካሪዎች ዘንድ ከፍተኛ የፍትሀዊነት ጥያቄ ሲያስነሳ የቆየውን የመንጃ ፈቃድ እግድ በትናንትናው እለት በይፋ ማቋረጡን የአዲስ አበባ ትራፊክ ማኔጅመንት ባለስልጣን አስታውቋል።
ባለስልጣኑ ይህንን ውሳኔ ያሳለፈው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 557/2016ን መሰረት በማድረግ ከተዘረጋው የዲጂታል የትራፊክ ቁጥጥር እና ቅጣት ማስፈጸሚያ ስርዓት አፈጻጸም ጋር በተያያዘ ነው።
በደንቡ መሰረት ተደጋጋሚ የደንብ መተላላፍ ፈጽመው የነጥብ ጣሪያ በመድረሳቸው ወይም በቆይታ ምክንያት የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫቸው ታግዶ እንደነበር ይታወቃል።
እንዲሁም ነጥባቸው ሳይሞላ አስቀድሞ ስልጠና ወስደው ነጥብ እንዲቀነስላቸው የሚፈልጉ አሽከርካሪዎች በደንቡ አንቀጽ 96 ንኡስ አንቀጽ 1 እና 2 መሰረት በሁለቱም የእውቅና ክህሎት ስልጠና ወስደው ማረጋገጫ ሲያቀርቡ እግዱ እንዲነሳላቸው ይደረጋል።
ይሁን እንጂ ይህ ሀገራዊ ደንብ በሀገሪቱ ሌሎች ክልሎች ባለመተግበሩ እና በአዲስ አበባ ከተማ በሚያሽከረክሩ ደንብ ተላላፊዎች ላይ ብቻ በመወሰኑ ሰፊ የፍትሀዊነት ጥያቄዎችን ፈጥሮ ነበር።
ይህንን የህዝብ ቅሬታ እና የፍትሀዊነት ጥያቄ የተገነዘበው የባለስልጣን መ/ቤት ጉዳዩን ለመንገድ ደህንነት ፈንድ አገልግሎት ባስታወቀው መሰረት፤ አገልግሎቱ በቁጥር 1904/18 እና በቀን 23/11/2018 በተጻፈ ደብዳቤ ምላሽ ሰጥቷል።
በሰጠው ምላሽም ከደንብ ትግበራ ጋር በተያያዘ ተደጋጋሚ ደንብ ተላላፊዎች የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ፈቃዳቸው ታግዶ የተሀድሶ ስልጠና የሚያገኙበትን ሂደት የተሳካ እና ፍትሃዊ ለማድረግ አጠቃላይ መመሪያ ሲዘጋጅ መቆየቱን አመላክቷል።
መመሪያውም ያሉበትን የማጽደቅ ሂደቶች አልፎ በአሁኑ ወቅት ለፍትህ ሚኒስቴር መላኩን እና በሀገሪቱ ሌሎች ክልሎችም ጭምር ወጥ የሆነ አሰራር ለመዘርጋት ሲባል ለጊዜው የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ፈቃድን የማገዱ ተግባር ሙሉ በሙሉ እንዲዘገይ ወስኗል።
በመሆኑም በደንብ መተላለፉ የሚከተሉት የገንዘብ ቅጣቶች ሙሉ በሙሉ እንደተጠበቁ ሆነው ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያው ጸድቆ እስኪላክ ድረስ ከትራፊክ ጉዳት ካደረሱ አሽከርካሪዎች ውጪ ለጊዜው በነጥብ እና በቆይታ (ሳይከፍል 6 ወር የቆየ) ምክንያት ከዚህ በፊት የታገዱትም ሆነ በቀጣይ ሊታገዱ የነበሩ የአሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ ፈቃዶች እግድ መቆሙን ባለስልጣኑ አረጋግጧል።
ባለስልጣኑ አክሎም አሽከርካሪዎች ከዚህ ቀደም ያነሱትን ጥያቄ መነሻ በማድረግ የታገደ መንጃ ፈቃድ በእጃቸው ያለና ያለባቸውን ሙሉ የቅጣት ክፍያ ያጠናቀቁ አካላት በአቅራቢያቸው ወደሚገኝ የባለስልጣኑ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት በመሄድ ማመልከት እና እግዱን ማስነሳት እንደሚችሉ ገልጿል።
ይሁን እንጂ ክፍያ ሳይጠናቀቅና እግድ ሳይነሳ ማሽከርከር ፍጹም የተከለከለ መሆኑን ባለስልጣኑ አሳስቧል።