የኢፌዲሪ የትምህርትና ስልጠና ባለሥልጣን የትምህርት ማስረጃ ማረጋገጫ እና የአቻ ግመታ መመሪያ ቁጥር 990/2016 ላይ ማሻሻያ ማድረጉን ይፋ አድርጓል።
ባለሥልጣኑ ይፋ ባደረገው በዚህ አዲስ ረቂቅ መመሪያ መሰረት እንደገና የሚፈተኑት ከ2010 እስከ 2015 ዓ.ም ባሉት ዓመታት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ እና በሦስተኛ ዲግሪ ተመርቀው የነበሩ ናቸው።
ይሁን እንጂ በወቅቱ የመውጫ ፈተና (Exit Exam) ሳይወስዱ ዲግሪያቸውን ያገኙ ተመራቂዎች የትምህርት ማስረጃቸውን ለማረጋገጥ ሲባል ዳግም እንዲፈተኑ የሚያስገድድ ድንጋጌ ተካቷል።
ባለሥልጣኑ በረቂቅ መመሪያው ላይ እንዳስቀመጠው ይህ ውሳኔ የተላለፈው የከፍተኛ ትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ እና የምሩቃንን የብቃት ደረጃ ወጥ በሆነ መንገድ ለመለካት ነው።
በዚህም መሰረት ቀደም ሲል ያለ መውጫ ፈተና ዲግሪ የያዙ ተመራቂዎች የትምህርት ማስረጃቸው እውቅና እንዲያገኝና እንዲረጋገጥላቸው ትምህርት ሚኒስቴር በሚያወጣው የብቃት ማረጋገጫ ፈተና ተፈትነው ማለፍ የግድ እንደሚሆንባቸው ረቂቁ በግልጽ ያሳያል።
የማሻሻያው ተፈጻሚነት ወሰን በተለይም ከ2010 እስከ 2015 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ እና በሦስተኛ ዲግሪ (BA, MA, and PhD) ተመርቀው የመውጫ ፈተና ያልወሰዱ ተመራቂዎችን እንዲሁም የደረጃ አራት የብቃት ማረጋገጫ (COC) ፈተና ሳይወስዱ ዲግሪ የተማሩትን ያጠቃልላል።
ባለሥልጣኑ በተጨማሪም ይህ ማሻሻያ በሥራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ ማንኛውም የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተማሪዎችን ሲቀበል ትምህርት ሚኒስቴር ወይም የሚመለከተው አካል የሚያወጣውን የመግቢያ መስፈርት ብቻ መከተል እንደሚኖርበት አጽንኦት ሰጥቷል።
ይህ እርምጃ የተወሰደው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ያለው የምረቃ ሂደትና የተመራቂዎች እውቀት ከሀገሪቱ የትምህርት ጥራት መስፈርት ጋር እንዲጣጣም ለማድረግ መሆኑን ያሰፈረው ባለስልጣኑ በስራ ገበያው ውስጥ ያሉ ምሩቃን ተወዳዳሪነትን እና የትምህርት ማስረጃን እውነተኛነት ለመጠበቅ የሚረዳ እንደሆነ አብራርቷል።
ባለሥልጣኑ ረቂቅ ማሻሻያው ላይ የባለድርሻ አካላትን አስተያየት ለመሰብሰብ ከሰኔ 29 እስከ ሐምሌ 13 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ክፍት የውይይት ጊዜ መመደቡን አስታውቋል።
በዚህም ፍላጎት ያላቸው ወገኖች አስተያየታቸውን በ https://forms.gle/ndRhodE2yoHSn2P5A ሊንክ በመግባት የዳሰሳ ጥያቄዎችን በመመለስ፤ በኢሜይል አድራሻ Info@eta.et በመላክ ወይም የረቂቅ ሰነዱን በባለሥልጣኑ ድረ-ገጽ www.neta.gov.et በመመልከት እንዲሰጡ ተጠይቋል።
በተጨማሪም ባለሥልጣኑ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ወገኖች በአካል ቀርበው አስተያየት እንዲሰጡበት የፊት ለፊት የውይይት መድረክ እንደሚያዘጋጅ ገልጾ የውይይቱንም ቀን፣ ሰዓት እና ቦታ በቀጣይ ቀናት እንደሚያሳውቅ አስታውቋል።
ይህ አዲስ መመሪያ በከፍተኛ ትምህርት ተመራቂዎች እና በተቋማት ዘንድ ከፍተኛ ውይይት ያስነሳል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ የታቀደው ይህ እርምጃ በምን መልኩ ተግባራዊ እንደሚሆን የሚታይ ይሆናል።