የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት ይፋ ባደረገው አጠቃላይ የሕዝብና ጤና ዳሰሳ ጥናት ኢትዮጵያ በጤና፣ በወሊድ መጠን፣ በትምህርት እና በሥራ ዕድል ዘርፎች መሠረታዊ ለውጦችን እያሳየች መሆኑን አስታውቋል።
እአአ በ2024 የተጀመረውና ለዘጠኝ ወራት የዘለቀው ይህ ጥናት፤ኢትዮጵያ ቀስ በቀስ ወደ ከተሞች መስፋፋት እና ዘመናዊ የቴክኖሎጂ አጠቃቀም እየተሸጋገረች መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎችን አካቷል።
የጥናቱ ውጤት እንደሚያሳየው ባለፉት 25 ዓመታት ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የሥነ-ሕዝብ ለውጥ የተመዘገበ ሲሆን ከሩብ ክፍለ ዘመን በፊት በአማካይ ስድስት የነበረው የአንዲት ሴት የወሊድ መጠን፣ በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ ከአራት በታች ወርዷል።
ሆኖም ይህ አማካይ መረጃ በከተማና በገጠር መካከል ያለውን ትልቅ ልዩነት የማያሳይ ሲሆን በአዲስ አበባ የወሊድ መጠኑ ወደ ሁለት ዝቅ ብሎ የመተካካት ደረጃ ላይ ሲደርስ በገጠር አካባቢዎች ግን አሁንም በአማካይ አምስት ነው።
የሕፃናት ጤናን በተመለከተ ጉልህ መሻሻሎች የታዩ ሲሆን ከ5 ዓመት በታች የነበረው የሕፃናት ሞት ከ1,000 ሕፃናት 166 ደርሶ የነበረው፤ አሁን ወደ 51 ዝቅ ብሏል።
ይህም የክትባት ዘመቻዎችና የተሻሻለ የጤና አገልግሎት ውጤት መሆኑን ጥናቱ ያመለከተ ቢሆንም አዲስ የተወለዱ ሕፃናት ሞት አሁንም ከፍተኛ ሆኖ ቀጥሏል። በተጨማሪም 68 በመቶ የሚሆኑ አዲስ የተወለዱ ሕፃናት በሕይወታቸው የመጀመሪያ ሳምንት ውስጥ የጤና ምርመራ እንደማያገኙ ጥናቱ አስታውቋል።
የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ሁኔታን በተመለከተ አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ (42 በመቶው) ከ14 ዓመት በታች የሆኑ ወጣቶች መሆናቸውን ገልጾ የመሠረታዊ አገልግሎቶች ተደራሽነት አሁንም ዝቅተኛ ነው።
57 በመቶ የሚሆነው ሕዝብ ንጹሕ የመጠጥ ውኃ አቅርቦት ያለው ሲሆን፤ 40 በመቶው ብቻ የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ነው የሚለው ጥናቱ ከሩብ በላይ የሚሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ አሁንም በሜዳ የመጸዳዳት ልማድ እንዳለው አስፍሯል።
የሥራ ዕድልን በሚመለከት 41 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች እና 87 በመቶ የሚሆኑት ወንዶች በሥራ ላይ እንደሚገኙ አሳይቷል።
አብዛኛው የሥራ ዕድል በግብርናው ዘርፍ ላይ የተመሠረተ ቢሆንም ከፍተኛ ቁጥር ያለው ዜጋ (56 በመቶ ሴቶችና 46 በመቶ ወንዶች) ደመወዝ አልባ ሥራዎችን የሚያከናውኑ መሆናቸው በግልጽ ተቀምጧል።
በመጨረሻም ጥናቱ በትራፊክ አደጋ ዙሪያ ካቀረበው መረጃ መረዳት እንደሚቻለው፤ በዓመት በአማካይ ከ3,000 እስከ 3,600 የሚደርሱ ሰዎች በትራፊክ አደጋ ሕይወታቸውን ያጣሉ።
ይህ ጥናት በሀገር አቀፍ ደረጃ በ19,460 ቀበሌዎች ውስጥ በተመረጡ 797 የመቁጠሪያ አካባቢዎች የተካሄደ ሲሆን ዩኤስኤአይዲ (USAID)፣ ግሎባል ፈንድ፣ ዩኬ ኤይድ፣ ዩኒሴፍ፣ ዩኤንኤፍፒኤ፣ የተባበሩት መንግሥታት ሴቶች ተቋም (UN Women) እና ጌትስ ፋውንዴሽን ድጋፍ አድርገውበታል።