ከአስር ዓመታት በፊት በነዳጅ እና በሊቲየም ፈጠራ ሥራቸው የብዙዎችን ትኩረት ስበው የነበሩት የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የኬሚስትሪ መምህር እና ተመራማሪው አቡሃይ ውብሸት ከአፈር ነዳጅ የማዘጋጀት ፈጠራቸው ስላለበት ወቅታዊ ሁኔታ ማብራርያ ሰጥተዋል።
ተመራማሪው እርሳቸውና ሌሎች ባልደረቦቻቸው የጀመሩት ይህ የምርምር ፕሮጀክት አሁን ላይ በላቦራቶሪ ደረጃ ከነበረበት የሚሊ ሊትር መጠን ከፍ ብሎ ከ30 እስከ 40 ሊትር ማምረት የሚያስችል ደረጃ ላይ መድረሱን በዝርዝር አስታውቀዋል።
ለዚህም አዲስ ፈጠራ የፈጠራ ባለቤትነት (ፓተንት) መብት የተሰጠ ሲሆን የኢትዮጵያ የጥራት ኤጀንሲም ምርቱ ለተሽከርካሪዎች አገልግሎት መዋል እንደሚችል የጥራት ማረጋገጫ እንደተሰጣቸው ከአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ጋር በነበራቸው ቆይታ አብራርተዋል።
በቀደምት ጊዜያትም በጎንደር ዩኒቨርሲቲ አማካኝነት ነዳጁ ተመርቶ የተወሰኑ ተሽከርካሪዎች አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ እንደተቻለና ከፕሮፌሰር ብርሃኑ አንዷለም ጋር በመሆን ለሠሩት አበረታች የምርምር ውጤት ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እውቅና እና ሽልማት እንደተበረከተላቸው ተመራማሪው አስታውሰዋል።
ለዚህ ሀገር በቀል ምርት ዋና ግብዓት የሆነው በሰሜን ተራራ የሚገኘው “ዶቤ” የተባለ የአፈር ዓይነት ሲሆን አፈሩን ከውኃ ጋር በመቀላቀል እና በተለያየ የሙቀት መጠን በማሳለፍ የተጣራ ነዳጅ ማግኘት እንደተቻለ ቀደም ሲል መዘገቡ ይታወሳል።
ይሁን እንጂ ይህ ትልቅ አቅም ያለው የፈጠራ ሥራ ሙሉ በሙሉ ወደ ፋብሪካ እና ሰፊ የጅምላ ምርት እንዳይሸጋገር የተለያዩ ተግዳሮቶች እንደገጠሙት ተመራማሪው ገልጸዋል።
ባለፉት ሁለት እና ሦስት ዓመታት በተለያዩ አካባቢዎች ተንቀሳቅሶ የጥሬ ዕቃ ናሙናዎችን ለማጥናት የጸጥታ ሁኔታው አስቸጋሪ መሆኑ፣ የፕሮጀክቱን አዋጭነት በሰፊው ለማጥናት እና ግብዓቱ በበቂ ሁኔታ መኖሩን ለማረጋገጥ የሚረዳ የፋይናንስ እጥረት ማጋጠሙ ተገልጿል።
በተጨማሪም ጎንደር ዩኒቨርሲቲ የተለያዩ እገዛዎችን እያደረገላቸው ቢሆንም በየጊዜው በሚደረጉ የአመራር ለውጦች ምክንያት በሚፈጠሩ አሠራሮች ውስጥ ተግዳሮቶች እንደገጠሟቸው ተመራማሪው አንስተዋል።
ምንም እንኳን ከፋብሪካ ማቋቋም አንጻር ሰፊ ምርት ላይ ለመድረስ የተለያዩ ተግዳሮቶች ቢኖሩም ፕሮጀክቱ ፍጹም እንዳልተቋረጠ እና በላቦራቶሪ ደረጃ ሥራው አሁንም እንደቀጠለ መምህር አቡሃይ አረጋግጠዋል።
ከባዮነዳጁ በተጨማሪም ለኤሌክትሪክ መኪናዎች እና ለወደፊት የኢነርጂ አቅርቦት ወሳኝ የሆነውን የሊቲየም ማዕድን ማውጣት ሥራ ላይ ትልቅ ውጤት መገኘቱን ጠቁመዋል።
በቀጣይ ለሙያው ቅርብ የሆኑ ባለሀብቶች፣ የመንግሥት አካላት እና በጎ አድራጊ ድርጅቶች በጥናት እና በፋይናንስ ቢደግፏቸው የጥሬ ዕቃ ክምችቱን አጥንተው ሙሉ በሙሉ ወደ ምርት ለመግባት ሙሉ ዝግጁነት እንዳላቸው ተመራማሪው ጥሪ አቅርበዋል።