የጋራ የቤት ባለቤትነትን በማስተዋወቅ የሚታወቀው ኬይ ሃውሲንግ ፋይናንስ ሶሉሽንስ ፒኤልሲ በ236 ተመዝጋቢ ገዢዎቹ ክስ እንደቀረበበት ተሰምቷል።
ከሳሾቹ የውል ስምምነታቸው በሕግ እንዲቋረጥ እና የ26.7 ሚሊዮን ብር መዋጯቸው እንዲመለስላቸው የጠየቁ ሲሆን በተጨማሪም ተመሳሳይ መጠን ያለው 26.7 ሚሊዮን ብር ካሳ እንዲከፈላቸው ጠይቀዋል።
በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሰኞ ዕለት የተጀመረው ይህ ክርክር የኩባንያው የኢንሹራንስ ጥበቃ አስተማማኝነት፣ የአባላት መዋጮ አጠቃቀም እና የቤቶች አቅርቦት ቃል ኪዳን የመፈጸም አቅም ላይ ጥያቄዎች የተነሱበት ነው።
የክሱ ዋና ማጠንጠኛ የኩባንያው ሞዴል "የፒራሚድ እቅድ" ይመስላል የሚለው የከሳሾቹ ውንጀላ ሲሆን ገዢዎቹ ኩባንያው ለቀድሞ ተሳታፊዎች የገባውን የቤት አቅርቦት ቃል ኪዳን ለመፈጸም በአዳዲስ አባላት መዋጮ ላይ ጥገኛ መሆኑን በመጥቀስ የውል አፈጻጸሙ አደገኛ መሆኑን ተከራክረዋል።
በተጨማሪም የቤቶች ክፍሎች ከተላለፉ በኋላም እንደ መያዣ ሊያገለግሉ እንደሚችሉ የሚደነግገው የውል አንቀጽ አባላትን ለከፍተኛ የንብረት አደጋ እንደሚያጋልጥ አመልክተዋል።
ከሳሾቹ በዋናነት የመረረ ቅሬታ ያቀረቡት በኢንሹራንስ ሽፋን ጉዳይ ላይ ሲሆን ኩባንያው ከቡና ኢንሹራንስ ጋር በነበረው አጋርነት ተስፋ ሰጪ ማስታወቂያዎችን ሲሰራ እንደነበር አስታውሰዋል።
ነገር ግን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አሰራሩን ተገቢ አይደለም ብሎ ከከለከለ በኋላ የገቡበት ውል ዋስትና እንደሌለው ገልጸዋል።
ምንም እንኳን ኩባንያው በኋላ ከኢትዮጵያ ኢንሹራንስ ኮርፖሬሽን ጋር አዲስ ስምምነት ቢፈጽምም ይህ ሽፋን ከቤት ርክክብ በኋላ የሚከሰቱ አደጋዎችን ብቻ የሚሸፍን እንጂ አባላት ቤቱን እስኪረከቡ ድረስ የሚከፍሉት መዋጮ በኩባንያው ቢከሰር ወይም ውሉ ቢቋረጥ ሊመለስ የሚችልበትን ዋስትና እንደማያካትት አስረድተዋል።
በሌላ በኩል ኬይ ሃውሲንግ ፋይናንስ ሶሉሽንስ ፒኤልሲ በጠበቃው አቶ ብርሃኑ ከፍያለው አማካኝነት የቀረበውን ክስ ውድቅ አድርጓል።
ኩባንያው የሚከተለው ከፒራሚድ አወቃቀር ፈጽሞ የተለየ "ሆሪዞንታል ስትራቴጂ" መሆኑን የገለጹት ጠበቃው፤ የኩባንያው ወደ ቤት ልማት መግባት የቤቶች ዋጋን ለመቀነስና አቅርቦትን ለማሳደግ ታቅዶ የተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
አባላት በባንክ በታገዱ ሂሳቦች ውስጥ መዋጯቸውን እንደሚያስቀምጡ የገለጹት አቶ ብርሃኑ፤ የቡና ኢንሹራንስን ክፍተት በባንክ ዋስትና እንደተተካ ተከራክረዋል።
ሆኖም በችሎቱ ላይ የኩባንያውን የአቅርቦት አቅም በተመለከተ ጥያቄ በተነሳበት ወቅት በሶስት ዓመታት ውስጥ ወደ 22,200 የሚጠጉ አባላት ተመዝግበው 600 ቤቶች ብቻ መተላለፋቸው የጊዜ ሰሌዳውን አጠያያቂ አድርጎታል።
በፕሮጀክቶች ላይ የዘገየው ምክንያት በመካከለኛው ምስራቅ ባለው ግጭት ምክንያት እንደሆነ ቢጠቀስም፤ የተለየ የግንባታ ሂደት መረጃ በችሎቱ አልቀረበም።
ፍርድ ቤቱ እስካሁን በክሱ ላይ ውሳኔ ያልሰጠ ሲሆን ኬይ ሃውሲንግ ፋይናንስ ሶሉሽንስ ፒኤልሲ የፒራሚድ እቅድ የተባለውን መዋጮ እንደተጠቀመ ወይም የውል ስምምነት እንደጣሰ በፍርድ ቤት እስካሁን አልተረጋገጠም።