የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸሙን አስመልክቶ በሰጠው መግለጫ በብልሹ አሰራር ተሳትፈው በተገኙ 62 የቢሮው አመራሮችና ሰራተኞች ላይ ጥብቅ እርምጃ መወሰዱን አስታወቋል።
በከተማዋ ሕጋዊ ንግድ ስርዓቱን ለማስከበር በተደረገው ርብርብም በሕገ-ወጥ ንግድ ላይ ተሰማርተው የተገኙ ከ24 ሺህ በላይ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃዎች መወሰዳቸው ተገልጿል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሀቢባ ሲራጅ የበጀት ዓመቱን አፈጻጸም ለህዝብ ይፋ ባደረጉበት ወቅት በተቋሙ ውስጥ የነበረው ሌብነት እና ብልሹ አሰራር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ መምጣቱን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል።
በቁጥጥር ስራውም ከታቀደው ዓላማ አንፃር በወንጀሉ እና በብልሹ አሰራሩ ውስጥ እጃቸው አለበት ተብሎ የተጠረጠሩ 62 ሰራተኞችና አመራሮች ተለይተው ተገቢው እርምጃ እንደተወሰደባቸው አስረድተዋል።
በከተማ አቀፍ ደረጃ አጠቃላይ የነጋዴዎች ቁጥር 470 ሺህ መድረሱን የገለጹት ወ/ሮ ሀቢባ ከንግድ ስርዓቱ የወጡ ወይም ዘርፍ የቀየሩ ነጋዴዎችን ቁጥር አብራርተዋል።
በዚህም መሰረት የንግድ ፈቃድ ሙሉ በሙሉ የመለሱ ወይም የንግድ ዘርፋቸውን የቀየሩ ነጋዴዎች ቁጥር 10 ሺህ እንደማይሞላ በግልጽ አስታውቀዋል።
የንግድ ማህበረሰቡን አሰራር ለማዘመን እና እንግልትን ለማስቀረት ባለፉት 5 ዓመታት በተከናወኑ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስራዎች 16 የንግድ ፈቃድና ምዝገባ አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል ስርአት መሸጋገራቸው ተመላክቷል።
በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት በዘመናዊ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አገልግሎት ዘርፍ በአጠቃላይ ከ706 ሺህ 800 በላይ አገልግሎቶች በኦንላይን መሰጠታቸውን ገልጸው፤ ከዚህ ውስጥ ከ105 ሺህ 700 በላይ አዲስ የንግድ ፈቃዶች፣ 339 ሺህ 784 የፈቃድ እድሳቶች ተደርገዋል ብለዋል።
ከዚህ ቀደም ነጋዴዎች አገልግሎቱን ለማግኘት ቀናትን ይወስድባቸው እንደነበር ያስታወሱት ኃላፊዋ አሁን ላይ አሰራሩ በመዘመኑ አጠቃላይ ሂደቱ ከ30 እስከ 40 ደቂቃ ብቻ እንደሚፈጅ ገልጸዋል።
በሌላ በኩል በከተማዋ በልማት ስራዎች ምክንያት ለተፈናቀሉ ነጋዴዎች ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱ የተነገረ ሲሆን በዚህ መሰረት በበጀት ዓመቱ ብቻ ለተፈናቀሉ ነጋዴዎች 5 ሺህ 556 አዳዲስ የንግድ ቦታዎች ተሰርተው መከፋፈላቸው ተመላክቷል።
በተጨማሪም በሕገ-ወጥ ተግባር እና አሰራር ላይ በመሳተፋቸው ምክንያት ከዚህ ቀደም ታሽገውና ተይዘው የነበሩ 524 የንግድ ሱቆች ተረጋግጦላቸው ለሚገባቸው ህጋዊ ባለቤቶች መተላለፋቸውን ቢሮው አስታውቋል።
በከተማዋ እየታየ ያለውን የዋጋ ንረት ለመቆጣጠር እና የምርት አቅርቦትን ለማሳደግ ትልቅ ፋይዳ ያላቸው ስራዎች መከናወናቸውም ተገልጿል።
ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በ15.9 ቢሊዮን ብር ወጪ ተገንብተው ወደ ስራ የገቡት 7 ዘመናዊ የግብርና ምርት መሸጫ ማዕከላት ናቸው።
እነዚህ ማዕከላት ሸማቾች ከ19.8 እስከ 25 በመቶ የሚደርስ የዋጋ ቅናሽ ያላቸው ምርቶችን በቀጥታ እንዲያገኙ በማድረግ የኑሮ ውድነቱን ለማረጋጋት ጉልህ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ ተጠቁሟል።