የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ በደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች የሚጠበቀው ዓመታዊ የግብር ገቢ በመንግስትና በግል ድርጅት ውስጥ ከሚገኙ ተቀጣሪ ደሞዝተኞች ዓመታዊ ደሞዝ ገቢ ግብር ጋር ሲነፃፀር በጣም አነስተኛ መሆኑን አስታውቋል።
ቢሮው ይህንን ያስታወቀ በደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች ዙሪያ ለሚዲያ ተቋማት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው።
የአስተዳደሩ ገቢዎች ቢሮ አነስተኛ የንግድ ስራ ላይ የተሰማሩ ግብር ከፋዮች እንዲበረታቱ፣ የግብር ጫና እንዳይደርስባቸውና ትርፋማነታቸውን በማጎልበት ወደ ቀጣይ ደረጃ እንዲሸጋገሩ ባለው ቁርጠኛ አቋም መሰረት ይህ አነስተኛ የግብር መጠን መወሰኑን በሰፊው አስረድቷል።
በከተማዋ በተለያዩ ንግዶች፣ በኪራይና በራይድ የንግድ ዘርፎች የተሰማሩ 456 ሺህ 433 የደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህ ግብር ከፋዮች በአጠቃላይ 9.2 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዷል።
ለተጠቃሚዎች የተላለፉ ጥሪዎችን እና የክፍያ ቀናትን በተመለከተ ቢሮው ማብራርያ የሰጠ ሲሆን እስከ ሐምሌ 25 መልዕክት የደረሳቸው ግብር ከፋዮች እስከ ሐምሌ 30/2018 ዓ.ም ድረስ የግብር ግዴታቸውን በኦንላይን በመክፈል ከቅጣትና ወለድ ራሳቸውን እንዲጠብቁ ጥሪ ቀርቧል።
ቴክስት ያልደረሳቸው ወይም ከሐምሌ 25 በኋላ መልዕክት የደረሳቸው አካላት ወደ ቅጣት የማይገቡ በመሆኑ እስከ ነሐሴ 20/2018 ዓ.ም ድረስ ዓመታዊ ግብራቸውን መክፈል እንደሚችሉ ተገልጿል። መልዕክት ያልተላከላቸው ግብር ከፋዮችም ባሉበት ሆነው በትዕግስት እንዲጠባበቁ ተመላክቷል።
በሌላ በኩል “ግብር በዛብኝ” የሚል ቅሬታ ላለው ማንኛውም ግብር ከፋይ ቅሬታ አፈታት ስርዓት መዘርጋቱ ነው የተገለፀው።
በዚህም መሰረት በወረዳ ደረጃ ቅሬታ ተቀብሎ በክፍለ ከተማ በተደራጀ የቀን ገቢ ገማች አማካኝነት ድጋሚ ግምት የሚሰጥበት ስርዓት ተዘጋጅቷል ተብሏል።
ለደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች በቴክስት የተላከው ዓመታዊ የግብር መጠን ከቅድመ ታክስ ክፍያ ጋር በተያያዘ ግብር ከፋዮች በቅድመ ታክስ የከፈሉትን የገንዘብ መጠን ተቀናሽ በማድረግ የተዘጋጀ መሆኑ በጋዜጣዊ መግለጫው ተመላክቷል።
ባለፉት ሁለት ዓመታት ፍትሐዊ የግብር አሰባሰብ ስርዐት ለመዘርጋት፣ መልካም አስተዳደርን ለማስፈን እንዲሁም የሌብነትና ብልሹ አሰራሮችን ለመቅረፍ ሰፋፊ ተግባራት መከናወናቸው ተጠቁሟል።
በተጨማሪም አብዛኞቹ የደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች በተዘረጋው የኦንላይን የክፍያ ስርዓት ክፍያቸውን መወጣታቸውና የተቀሩትም እየከፈሉ መሆኑ ተገልጿል።
በመጪው 2019 በጀት ዓመት እንደ ከተማ 502.27 ቢሊዮን ብር፣ በገቢዎች ቢሮ በኩል ደግሞ 380 ቢሊዮን ብር ገቢን በፍትሐዊነት ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝ ተጠቁሟል።