በአዲስ አበባ የሚገኙ ትምህርት ቤቶች መከፈትን ተከትሎ ከወትሮው የተለየ የትራፊክ ፍሰትና መጨናነቅ እንደሚስተዋል የከተማዋ ትራፊክ ማኔጅመንት ባለሥልጣን አስታውቋል።
ተቋሙ አዲሱን የትምህርት ዘመን መነሻ በማድረግ በትምህርት ቤቶች ዙሪያ የሚፈጠሩ የትራፊክ መጨናነቆችን ለመቅረፍ ጥብቅ የቁጥጥር ማዕቀፎችንና የዝግጅት ሥራዎችን ማጠናቀቁን ይፋ አድርጓል።
በዚህም በመዲናዋ በትምህርት ቤቶች መግቢያና መውጫ ሰዓት ማንኛውንም ተሽከርካሪ በዋና መንገዶች ላይ ደርቦ ማቆም በጥብቅ እንደሚያስቀጣ ባለሥልጣኑ አስታውቋል።
ወላጆች ተሽከርካሪዎችን መንገድ ላይ ለሰከንዶች ብቻ አቁመው ተማሪዎችን ማውረድ እንደሚችሉ የተጠቆመ ሲሆን፤ ነገር ግን ተሽከርካሪን ለደቂቃዎች በአካባቢው ማቆምም ሆነ አቁሞ ማውረድ ፍጹም የተከለከለ እና የ1 ሺህ ብር ቅጣት የሚያስከትል ሕገወጥ ተግባር መሆኑን ባለሥልጣኑ አሳስቧል።
የዚህን ችግር ስፋት በዘላቂነት ለመቀነስ ከግል ተሽከርካሪዎች ይልቅ ተማሪዎች በትምህርት ቤት ሰርቪስ እንዲጓዙ ከትምህርት ቤቶች ጋር ስምምነት መደረጉ ተመላክቷል።
በተጨማሪም ከዋና መንገዶች ውጪ ያሉ መንገዶችን ለመግቢያና ለመውጫነት እንዲጠቀሙ ስምምነት መደረጉ የተነገረ ሲሆን አሽከርካሪዎችም ተማሪዎችን በፍጥነት አውርዶ የመንዳት አሰራርን በመከተል ተማሪዎችን ለመምህራንና ለረዳቶች እንዲያስረክቡ ጥሪ ቀርቧል።
በሌላ በኩል በ2019 የትምህርት ዘመን መጀመር ምክንያት ተመሳሳይ የትራፊክ ችግሮች እንዳይፈጠሩ ከማዕከል እስከ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች አጠቃላይ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን የባለስልጣኑ የመንገድ ደህንነት ግንዛቤ እና ቁጥጥር ዘርፍ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ አማረ ታረቀኝ ገልጸዋል።
ከክረምት ወራት በኋላ ትምህርት ሲጀመር በትምህርት ቤቶች አካባቢ ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ እንደሚፈጠር ያስታወሱት ኃላፊው ችግሩን ለመቋቋም ከወዲሁ ሰፊ ዝግጅት መደረጉን አብራርተዋል።
እንደ አቶ አማረ ገለጻ ለአደጋ ተጋላጭነት አላቸው ተብሎ በተለዩ ትምህርት ቤቶች የተማሪ ትራፊኮች ቀድመው በመገኘት ተማሪዎችን እንዲያስተባብሩ የሚደረግ ሲሆን የቁጥጥር ባለሙያዎች እና የበጎ ፈቃደኛ ትራፊክ አስተባባሪዎች በተደራቢነት ተሰማርተዋል።
ተቋሙ በየዓመቱ ከ500 እስከ 1 ሺህ የሚደርሱ በጎ ፈቃደኛ ተማሪዎችን በትራፊክ ማስተናገድ ሥራ ላይ በማሰልጠን ድጋፍ ሲሰጥ መቆየቱን የተገለጸ ሲሆን ዘንድሮም እነዚህ በጎ ፈቃደኞች በትምህርት ቤቶች አካባቢ ተጨማሪ ድጋፍ እንዲሰጡ ይደረጋል ተብሏል።
በምህንድስና ዘርፍም የምልክት ተከላ፣ የእግረኛ መንገዶች እድሳት እና የዜብራ ቀለም ቅብ ሥራዎች መከናወናቸውን ባለሥልጣኑ ገልጿል።
ከዚህም በተጨማሪ በትምህርት ቤቶች አካባቢ የተሰማሩ የሕዝብ ትራንስፖርቶችና የተማሪ አውቶቡሶች ቅድሚያ እንዲያገኙ የማስተባበር ሥራ ይሠራል ያሉ ሲሆን ረድፎችን አለመጠበቅ፣ ደርቦ መጫንና ማውረድ በደንብ 557/2016 በእርከን 2 ቁጥር 4 መሠረት ጥብቅ ቁጥጥር የሚደረግበት መሆኑ አመላክተዋል።
ባለሥልጣኑ ከትምህርት ቤት አመራሮች፣ ከወላጅ ኮሚቴዎችና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የጀመረውን ጥብቅ የቁጥጥርና የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጧል።