በኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ከተማ አቅራቢያ የሚገኘውና በ330 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የሚገነባው የቱሉ ካፒ የወርቅ ማዕድን ፕሮጀክት ይፋዊ የግንባታ ሥራውን መጀመሩ ተገልጿል።
በዓመት በአማካይ 166 ሺህ ኦውንስ ወርቅ ያመርታል ተብሎ የሚጠበቀው የኬፊ ጎልድ ኤንድ ኮፐር ኩባንያ 'የቱሉ ካፒ' የወርቅ ማዕድን ፕሮጀክት በጸጥታ እና ጂኦፖለቲካዊ ቀውሶች ምክንያት ከ6 እስከ 7 ዓመታት ገደማ ተጓትቶ እንደነበር ተገልጿል።
ከ400 ሚሊዮን ዶላር በላይ የፋይናንስ ፓኬጅ የተመደበለት ፕሮጄክቱ የኢትዮጵያ መንግስት 20 ሚሊዮን ዶላር በማዋጣት የ17 በመቶ ድርሻ ይዟል ተብሏል።
ማዕድን ማውጣቱ ክፍት እና ከመሬት በታች የማውጣት ዘዴዎችን አጣምሮ የሚጠቀም ሲሆን በ2027 መገባደጃ ላይ ስራ ጀምሮ በ2028 ሙሉ የማምረት አቅሙ ላይ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል።
የKEFI ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሃሪ አናኖስታራስ-አዳምስ የቱሉ ካፒ ፕሮጀክት ለኢትዮጵያ የስትራቴጂካዊ ፕሮጀክት ነው ያሉ ሲሆን በቀጣዩ አስር ዓመት የማዕድን ዘርፉ ለሀገሪቱ ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ በአሁኑ ወቅት ካለበት 1 በመቶ ወደ 10 በመቶ ከፍ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ዋናውን ሚና ይጫወታል ብለዋል።
እንደዘገባው ከሆነ ፕሮጄክቱ እ.ኤ.አ በ2013 KEFI 75 በመቶ ድርሻውን ከኒዮታ ሚነራልስ (’Nyota Minerals’) የገዛው ቢሆንም በ2014 የቀረውን ድርሻ በመግዛት የፕሮጀክቱን 100% ባለቤትነት ተቆጣጥሯል።
በ2015 በወቅቱ ዝቅተኛ በነበረው የወርቅ ዋጋ መሠረት የተሻሻለ የአካባቢና የኢኮኖሚ ጥናት ከተካሄደ በኋላ የማዕድን ማውጣት ፈቃድ ተሰጥቷል።
ይሁን እንጂ ባለፉት ዓመታት በነበሩት የጸጥታና የጂኦፖለቲካዊ ቀውሶች እንዲሁም የገንዘብ ድጋፍ ፈተናዎች ለፕሮጄክቱ መዘግየት ምክንያት መሆናቸው ተገልጿል።
ሆኖም አሁን ላይ የገንዘብ ድጋፉ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁንና የኢትዮጵያ መንግሥት በየደረጃው ከፍተኛ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ኩባንያው በመግለጽ በቅርቡ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ እና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ በተገኙበት የመሠረት ማስቀመጣቸውን አውስቷል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በወቅቱ ፕሮጀክቱ በመንግሥትና በግል ኢንቨስተሮች ትብብር የሚሰራ መሆኑን በመጥቀስ “የቱሉ ካፒ የወርቅ ልማት ፕሮጀክት የተፈጥሮ ኃብታችንን እንዴት ለሀገር እና ሕዝብ ጥቅም በኃላፊነት ልንጠቀምበት እንደምንችል የሚያሳይ አይነተኛ ምሳሌ ነው” ሲሉ ገልጸዉታል።
ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ የሚሆን ከ400 ሚሊዮን ዶላር በላይ የፋይናንስ ፓኬጅ መዘጋጀቱን ኩባንያው ያስታወቀ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት 17 በመቶ ድርሻ እንዳለውም ገልጿል።
ዋና ስራ አስፈጻሚው አናኖስታራስ-አዳምስ ኢትዮጵያ በቱሉ ካፒ እና በኩርሙክ ፕሮጀክቶች ላይ በመመስረት በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ የወርቅ አምራች ሀገር ሆና የመውጣት ትልቅ ዕድል አላት ማለታቸውን ማይኒንግ ሪቪው አፍሪካ ዘግቧል።
ከ6 እስከ 7 ዓመታት ተጓትቶ የነበረው የቱሉ ካፒ የወርቅ ፕሮጀክት ወደ ሥራ ገባ
አጋራ፦
ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ የሚሆን ከ400 ሚሊዮን ዶላር በላይ የፋይናንስ ፓኬጅ መዘጋጀቱን ኩባንያው ያስታወቀ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት 17 በመቶ ድርሻ እንዳለውም ገልጿል።